Web Toolbar by Wibiya

Follow Us

የኦህዴድ ክፍፍል ወደ ዞን ባለስልጣናትም ወረደ

ጥቅምት ፳፯ (ሀያ ሰባት) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም
ኢሳት ዜና:-የኦህዴድ ክፍፍል ወደ ዞኖች ወርዷል፣ ይህን መንግስት ተቀብለን እንቀጥላለን ወይም አንቀጥልም የሚሉ ሁለት ቡድኖች መፈጠራቸውን አባላቱ ገለጡ
ስማቸው እንዳይገለጥ ያስጠነቀቁ የኦህዴድ ባለስልጣናት ለኢሳት እንደገለጡት በኦህዴድ ከፍተኛ አመራሮች የተፈጠረው መከፋፈል ወደ ዞኖች ወርዶ በድርጅቱ ውስጥ ሁለት ቡድኖች እንዲፈጠሩ አድርጓል።

ከፍተኛ ክፍፍል በሚታይበት በሀረሪ ክልል ፣  በአንድ በኩል ይህንን ስርአት ደግፈን መጓዝ አለብን የሚሉ  ኦህዴዶች ደጋፊዎችን ለማሰባሰብ ሙከራ በማድረግ ላይ ሲሆኑ፣ በሌላ በኩል ደግሞ ” ብዙሀን እንዴት በአናሳ ቡድን ይገዛሉ? ” በማለት ስርአቱን አንቀበልም ያሉ ሀይሎች የራሳቸውን ደጋፊ በማሰባሰብ ቡድን እየፈጠሩ ነው።

“ብዙሀኑ በአናሳ አይገዙም ” የሚለውን ሃሳብ እያቀነቀኑ የሚገኙት የኦህዴድ አባላት ፣ የጠቅላይ ሚኒስትርነት ወይም ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትርነት ቦታ ለኦህዴድ አለመሰጠቱ፣ “ኦህዴድ መሳሪያ ነው እንጅ ምንም ስልጣን የለውም” የሚል ስሜት እንዲያድርባቸው ማድረጉን ባለስልጣናቱ ተናግረዋል።

ክፍፍሉን ተከትሎ በተለይ በሀረሪ ፣ ክልሉን ማን ያስተዳድረው የሚለው ጥያቄ እንደገና ማገርሸቱንና የኦሮሞ ተወላጆች  ጥያቄውን እየገፉበት እንደሚገኙ ለማወቅ ተችሎአል።

የኦህዴድ መከፋፈል ድርጅቱን ምን ያክል እንደሚጎዳው ለመገመት አስቸጋሪ ቢሆንም፣ አዲሱን ስርአት የሚቃወሙት አባላት ቁጥር እየጨመረ መምጣቱን ባለስልጣናቱ ይናገራሉ።

በኦህዴድ ውስጥ ያለው ክፍፍል እና ቅሬታ አዲሱ ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ ሀይለማርያም ደሳለኝ እስካሁን ድረስ ካቢኔያቸውን ለመሾም እንዳላስቻላቸው መዘገቡ ይታወሳል።

በሌላ ዜና ደግሞ በሀረሪ ክልል ልዩ ስሙ ደከር በሚባል ቦታ አቶ ጀማል የተባሉትን ባለሀብት የፌደራል ፖሊሶች በምሽት በመውሰድ ከፍተኛ ድብደባ በመፈጸም አስረዋቸዋል።
ፖሊሶቹ ባለሀብቱን “ድሮ በኦነግ አሁን ደግሞ በሀይማኖት መጣህ” በማለት እየደበደቡ እንደወሰዱዋቸው አይን እማኞች ለኢሳት ገልጠዋል።
06, Novemeber 2012
ESAT NEWS.

0 comments: